Monday, December 13, 2010

ስብከተ አሰጋሽ


የዛሬው ነገሬን የምወስደው ከ ዳኛቸው ወርቁ “አደፍርስ” ነው፡፡ ምናልባት መጽሐፉን የማታውቁ ሰዎች ካላችሁ ኢትዮጵያ ውስጥ ከተጻፉት ምርጥ ልቦለዶች አንዱ ነው፡፡ የተጻፈበት ዘመን ትንሽ ራቅ ስለሚል (1962 ዓ.ም.) ለማግኘት በጣም አስቸጋሪ እንደሆነ ከወዲሁ ልጠቁማችሁ እወዳለሁ፡፡ ይሁንና እንደው በአንዳች ተአምር መጽሐፉ እጃችሁ ከገባ አደራ የከፈላችሁትን ከፍላችሁ ከመግዛት ወደኋላ እንዳትሉ፡፡ መጀመሪያ አይታችሁት የሚገፋተር ከመሰላችሁ እንዳትሸሹ አደራ፡፡

በነገራችን ላይ የቴዎድሮስ ገብሬን “በይነ- ዲሲፕሊናዊ የሥነ ጽሑፍ ንባብ” የሚለውን መጽሐፍ ብታነቡት አደፍርስን “በአንድምታ” ትረዱታላችሁ፡፡ በኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ጀርናል ላይ የታተመለትን “አደፍርስ ዘመናዊው ልቦለድ” የተሰኘውን መጣጥፉን ብታነቡም የበለጠ ታጣጥሙታላችሁ፡፡

ለዛሬ ወ/ሮ አሰጋሽ የሚባሉ ገጸ ባሕርይ ከሚናገሩት ንግግር እግዜርን እንዴት እንደሚበይኑት እንመልከት፡፡ እንደኔ እንደኔ ብዙ ሰው እግዚአብሔርን እንደ ወ/ሮ አሰጋሽ የሚመለከተው ይመስለኛል፡፡

“እግዜር ሩቁን የማያይ ይመስልሃል? ተሳስተሃል ወንድሜ፤ እግዚአብሔርን ርቀትና ቅርበት አይወስነውም፡፡ እግዚአብሔር እዚህ እዚያ እሁሉ ቦታ ነው- አሁን ከኛ ጋር ነው ስንነጋገር- ሁሉን ይሰማል- ሁሉን ያያል- ሁሉን ያውቃል፡፡ አዎ፣ አንዳንዴ የማያይ፣ የማይሰማ፣ የማያውቅ መስሎ መታየትን ይመርጣል፡፡ የበደሉትን ሰዎች እግር ተንበርክኮ ያጥባል- እንደፈለጋችሁ- እንደምላዳችሁ- እንደስሜታችሁ ኑሩ የሚል ይመስላል፣ ለብልኀቱ፡፡ አንድ ቀን የሱን ትልቅነት፣ የሱን ወሰን የለሽነት፣ የሱን አይመረመሬነት ዘንጋ ያልን ጊዜ ድራሻችንን ሊያጠፋ፡፡ ሊያመጣው ውርጅብኙን፡፡- ሥልጣናችሁን በሚገባ አልተጠቀማችሁበትም- ለክብሬ የሚገባኝን አላቀረባችሁልኝም- ከየምታገኙት ገንዘብ ጥቂት ጥቂት እያነሣችሁ- ጧፍ ዕጣን፣ ጋድና ሻማ፣ መገበሪያና ጃንጥላ በማቅረብ ፈንታ በሙሉ ተጫወታችሁበት- ጠጅ መሰርገቢያና በገሰቢያ አደረጋችሁት- ስለዚህ እኔም የምሠራውን አውቃለሁ ሊለን- መጠጡ ራሳችሁን እያብረጀረጀ ከሳንቃ ጉበን እንዲደስማችሁ፣ አንበጣ፣ አመዳይና ቸነፈር የምትበሉትን አሳጥተው ችጋር እንዲነዙባችሁ- ተጓባቢውን ጎረምሳ፣ ጥጋብ የነፋውን፣ በዱላ የሚጎላመደውን ዱለኛ፣ ለባለ ርስቱ ለባላባቱ የማይታዘዘውን ገበሬ፣ አንገቱን ሰብረው ጭራውን እንደውሻ እንዲሸጉብ እስኪያደርጉት ድረስ- ሊለን! ሊያመጣው የጭቃ ጅራፉን…” ይላሉ ወይዘሮ አሰጋሽ ለአንዱ ጭሰኛቸው-

Friday, November 26, 2010

ግጥም ስናጣጥም Enjoying Amharic poetry

ገጣሚ፡- ገብረ ክርስቶስ ደስታ           

(መንገድ ስጡኝ ሰፊ፣ ገጽ 62)

የዓለም መራራነት

ያለም መራራነት ነው የሚጣፍጠን
መቸ መጣፈጧ፤
ኮሶውን በማሯ ጠቅልላ ስትሰጠን
        ስትሰጠን እሳቱን
አመድ አስመስላ ሸፍና ረመጡን፡፡
ስትሰጥ ማየ ሕይወት ስትሰጠን መድኃኒት
መርዟ ጨምራበት፡፡
ስትሰጠን እሬቱን ስኳር አስመስላ
እንደጎመን ሠርታ ሳማዋን ስንበላ፡:
                                
                                እሷ ትዞራለች
                                ፀሐይ ትሞቃለች
እኛን በብርድ ላይ በጨለማ ጥላ፡፡
ያለም መራራነት
የሚያቆራምድ ነው፤ የሚያኮራምት፡፡
ስትወስድ ወደኋላ ስትወስድ ወደ ሌላ
ምሥጢር ያላት መስላ፡፡
ከቤተሰብ ማሕል
ሰው ስታስኮበልል፡፡
ስትወስድ ስጦታዋን
ለገጸበረከት ያቀረበችውን፡፡
ሌባ ናት ሰራቂ
ቀጣፊ ነጣቂ፡፡
አቀባባይ ቀልማዳ፤ አታላይ አስመሳይ
ዋሾ ናት ወላዋይ፡፡
ሰው ሊኖር ባለም ላይ መች ተፈጠረ!
መንገደኛ እንግዳ
መሽቶበት የመጣ
ሠራተኛ አገልጋይ ነው የተቸገረ፡፡
ብዙ ነው ልፋቱ
ሲፈጠር፤ ሲመጣ፤ ሲወጣ ከቤቱ፡፡
አይችልም መዝናናት
በደመነፍስ ባሕርይ እንደተቀረጹት፡፡
እንዳህያ እንደጅብ ወይም እንደጦጣ
ወይም እንዳንበጣ
የማይቸገሩት ለምን ያስባሉ?
ከብቶች ይግጣሉ፤ ወፎች ይዘፍናሉ
አበቦች ያድጋሉ፡፡
ውስጡን አላወቁም፤ አልተመራመሩም
ሲመጡ ወዳለም፡፡
የውሸት ሥዕል ናት
                                ለዛዋ እሚጠፋ ቀለሟ እሚጠፋ፡፡
ጠረኗ እሚያባርር፤ ጣሟ እሚከረክር
ቧልቷ የሚያስመርር፡፡
የሰው ልጅ አንድ ባንድ ልታንሸራሽረው
ሁልጊዜ እንግዳ ነው
ማናፈስ ማቅበጧ
ማቻኮል ማሮጧ፡፡
ያለም መራራነት ነው የሚጣፍጠን
                                መቸ መጣፈጧ! 





የግጥም ልክፍተኛው ወዳጄ ሲሳይ ጫን ያለው ሬድዮ ፋና ላይ “ግጥም እናጣጥም” የሚል ድንቅ ዝግጅት ይዞላችኋል፡፡


By the way,
I got the pictures from the internet.
The man on the photograph is Gebrekirstos himself. The title of the painting below the poem is Patriots. <the3rdman.com>